ከነሐሴ 16 ቀን 2007 ዓ.ም. ጀምሮ በመቐለ ሰማዕታት አዳራሽ እየተደረገ ባለው 12ኛው የሕወሓት ጉባዔ፣ በመተካካት ስም በሟቹ መለስ ዜናዊ ምክንያት ተሸኝተው የነበሩ የሕወሓት አመራሮች በጉባዔው እንዲመረጡና እንዲመርጡ ተወሰነ፡፡ ሪፖርተር እንዳለው አዘጋጅ ኮሚቴው የጋበዛቸው ያለ ድምፅ እንዲሳተፉ ነበር፡፡
ከ1,650 በላይ ጉባዔተኞች በታደሙበት ጉባዔ የተገኙ አንድ ተሳታፊ ከዚህ ቀደም ተገፍተው የወጡ ያሏቸው ነበር አመራሮች በድምፅ እንዲሳተፉ ጥያቄ ካቀረቡ በኋላ፣ በጉዳዩ ላይ የመከረው ጉባዔ በጭብጨባ በሙሉ ድምፅ ጥያቄውን ተቀብሎታል፡፡ በዚህም መሠረት ዶ/ር አርከበ እቁባይ፣ አቶ ስብሃት ነጋ (አቦይ)፣አምባሳደር ሥዩም መስፍን፣ አምባሳደር ብርሃነ ገብረ ክርስቶስ፣ አቶ ፀጋዬ በርኼን ጨምሮ 17 ነባር አባላት ተሳታፊ ሆነዋል፡፡
ጉባዔው በእስካሁኑ ቆይታው በአንደኛው የዕድገትና የትራንስፎርሜሽን ዕቅድ፣ በመልካም አስተዳደርና በመተካካት ላይ ተወያይቷል፡፡ ያለው ሪፖርተር በመልካም አስተዳደር እጦት ክልሉ እየተጠቃ እንደሆነ በርካታ አስተያየቶች ተሰጥተዋል ብሏል፡፡ በተለይ በአንድ የሃይማኖት አባት የቀረበው የመልካም አስተዳደር እጦት ትኩረት የሳበ ነበር፡፡ የሕወሓት አመራሮች ድርጅቱ ቀድሞ አንግተውት የነበረውን ዓላማ እንደረሱ በአጽንኦት ገልጸው፣ ፍትሕ በገንዘብ እየተገዛ የክልሉ ሕዝብ የማያውቀው አዲስ ባህል በመጎልበቱ ይህንንም እንደሚዋጉት አመልክተዋል፡፡ ‹‹እሳት ያልፈራ ሕዝብ እናንተን የሚፈራ ይመስላችኋል?›› ሲሉም ጥያቄአቸውን አቅርበዋል፡፡ መተካካትን በተመለከተም ወደ መገፋፋት በመቀየሩ ያለ ዕድሜና አቅም ማነስ ዶ/ር አርከበና አምባሳደር ብርሃነ እንዲወጡ መደረጉን ተችተዋል ብሏል ሪፖርተር
እንደ ድሮው መገማገምና አንዱ አንዱን ተጠያቂ ማድረግ በመሸፋፈንና በመጠባበቅ መቀየሩም ተገልጿል ሲል ገልጿል።
የሕወሓት ሊቀመንበርና የክልሉ ፕሬዚዳንት አቶ ዓባይ ወልዱ የቀረበውን ቅሬታ ተቀብለው፣ የተሠራ ነገር ቢኖርም ትልቅ ዳገት እንደሚጠብቅ ገልጸዋል፡፡ የአመራር አባላት ራሳቸውን ማጥራትና ወደ ራሳቸው መመልከት እንደሚኖርባቸው አሳስበዋል፡፡
ዶ/ር አርከበ በጉባዔው ንቁ ተሳትፎ ያደረጉ ሲሆን፣ ሕዝቡ ቅሬታ እያቀረበ ያለው በፍትሕ አካላትና በፓርቲው አባላት መሆኑ አሳሳቢ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡
ጉባዔው ዛሬ የሚጠናቀቅ ሲሆን፣ የሥራ አስፈጻሚና የማዕከላዊ ኮሚቴ እንዲሁም የቁጥጥር ኮሚሽን አባላትን ይመርጣል ብሏል። በዜናው ዙርያ አስተያየት የጠየቅናቸው የፖለቲካ ተንታኝ “የመለስ ርዕዬ የሚሉት ከቃል ያልዘለለ መሆኑን ማሳያ ነው የሚሉት ተንታኙ ጠቅላይ ሚኒስቴሩ ከመሞታቸው አስቀድሞ በመተካካት ሰበብ ያስወገዷቸውን መመለስ ሁለት ነገሮችን ያሳያል አንደኛው የስርዓቱን አንባገነንነት ከነሱ ውጪ ለማስቀጠል በወጣቱ ላይ እምነት ማጣታቸውን ፤በሌላ በኩል ህዝብን የመለስ ርዕዬ እያሉ በተግባር የአቶ መለስን አንባገነንነት እየገለፁ በወቅቱ የወሰነው
ውሳኔ ተገቢ አለመሆኑን አሳይተዋል ይህ ደግሞ አፍቃሪ መለስ ለሆኑ አባላትን አንገት ለማስደፋት በፓርቲው ውስጥ መከፋፈል እንዳለ ያሳያል ብለዋል። ተባረው የነበሩትን የድርጅቱ ነባር መሪዎች የመለሰው ህወሓት 7 ዓባላቱን ከማእከላዊ ኮሚቴ አባልነት ዛሬ አሰናብቷል።
አቶ አባይ ጸሃዬ፣ አቶ ቴዎድሮስ ሀጎስ፣ አቶ አባዲ ዘሙ፣ አቶ ጸጋዬ በርሄ፣ ወይዘሮ ሮማን ገብረስላሴ፣ አቶ ተወልደ በርኸ እና አቶ ተክለወይን አሰፋን ከህወሃት ማእከላዊ ኮሚቴ አባልነት በክብር እንዲሰናበቱ ተደርጓል።
በተያያዘ ዜና ብአዴንና ኦሕዴድ ሰሞኑን ባካሄዱዋቸው ጉባዔዎቻቸው ሊቀ መንበሮቻቸውንና ምክትል ሊቀመንበሮቻቸውን መረጡ፡፡
ከነሐሴ 17 ቀን 2007 ዓ.ም. ጀምሮ ሲካሄድ የነበረው 11ኛው የብሔረ አማራ ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ (ብአዴን) ድርጅታዊ ጉባዔ አቶ ደመቀ መኮንን በድጋሚ የድርጅቱ ሊቀመንበር አድርጎ ሲመርጥ፣ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አቶ ገዱ አንዳርጋቸውን ደግሞ ምክትል ሊቀመንበር አድርጎ መርጧል፡፡
ጉባዔው ከዚህ በተጨማሪም ዘጠኝ የኢሕአዴግ የሥራ አስፈጻሚ አባላትንና 13 የብአዴን ሥራ አስፈጻሚ አባላትን ምርጫም አከናውኗል፡፡
በዚህም መሠረት አቶ ደመቀ መኮንን፣ አቶ ገዱ አንዳርጋቸው፣ አቶ ዓለምነው መኮንን፣ አቶ ብናልፍ አንዱዓለም፣ አቶ ተስፋዬ ጌታቸው፣ ዶ/ር አምባቸው መኮንን፣ አቶ አህመድ አብተው፣ አቶ ከበደ ጫኔና አቶ ካሳ ተክለ ብርሃን የኢሕአዴግ ሥራ አስፈጻሚ አባላት ሆነው ተመርጠዋል፡፡ የኢሕአዴግ ሥራ አስፈጻሚ ሆነው የተመረጡትን ጨምቶ አቶ ተፈራ ደርበው፣ አቶ ጌታቸው ጀምበር፣ አቶ ለገሰ ቱሉና ዝማም አሰፋ ደግሞ የብአዴን ሥራ አስፈጻሚ አባል ሆነው ተመርጠዋል፡፡
የኦሮሞ ሕዝብ ዴሞክራሲያዊ ድርጅት (ኦሕዴድ) አቶ ሙክታር ከድርን በሊቀመንበርነት፣ ወ/ሮ አስቴር ማሞን በምክትል ሊቀመንበርነት መርጧል፡፡ በተጨማሪም 81 የማዕከላዊ ኮሚቴ አባላትና 15 የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባላት ተመርጠዋል፡፡