ይድረስ በውጭ ጉዳይ ሚኒስትር የሴቶች ጉዳይ
ዳይሬክቶሬት ለዶር ደስታ ወ/ጊዮርጊስ
ለሁለተኛ ጊዜ ለቀናት ጉብኝት የውጭ ጉዳይ ትልቅ እንግዳ የሆኑት እርስዎ መምጣትዎን ሰምቻለሁ ፣ አምና ለተመሳሳይ ጉብኝት መጥተው ባረፉበት ሆቴል ተገናኝተን በሳውዲ ስደተኛ ስላለው ነባራዊ ሁኔታ፣ በተለይም በብላቴናው መሀመድና በአንድ የሳውዲ እስር ቤት ግፍ በተሰራበት ኢትዮጵያዊ ዙሪያ የፎቶ መረጃ አቅርቤ ሳጫውትዎ ተያይዘን ማልቀሳችን አይረሳኝም … ከዚያ ወዲህ አደርገዋለሁ ያሉት ሆኖ የማየት እድል ባይገጥመኝም ፣ ከፍ ያሉ የመንግስት ኃላፊ ነዎትና የዛሬም አጭር መልዕክቴን ላደርስዎ ግድ አለኝ …
ክብርት ዶር ደስታ ሆይ ፣ ገና 4 ዓመት ህጻን እያለ ግፍ ተፈጽሞበት ከሪያድ ኢንባሲ እስከ ጅዳ ቆንስላ ተወካዮች ለአመታት ድጋፍ ያላደረጉላቸውን የብላቴናው ቤተሰቦች የመጎብኘቱ እድል አሁንም እንዳምናው ዘንድሮም እንዳያመልጥዎ ፈራሁ … ይገርምዎታል ዛሬ ማለዳ ላይ ቀንቶን ሁለቱም ታዋቂ እለታዊ የእንግሊዝኛ ጋዜጦች አረብ ኒውስና ሳውዲ ጋዜጥ በሀኪሞች ስህተት ላለፉት 9 ዓመታት የተኮላሸ ፣ የተሰናከለውን ብላቴናውን መሀመድ አብድልአዚዝ አበሳና የእናቱን አቤቱታ በተገቢ መንገድ አስተናግደውልናል ! ጋዜጣው በማለዳው በእርስዎ ክፍል እንደደረሰዎምና እንደተመለከቱት እገምታለሁ ፣ መረጃው በሰፊው ሲሰራጭ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ዜጎች በአለም ዙሪያ የብላቴናውን መሀመድን በደል ሰምተው አዝነዋል ፣ #JusticeForMohammed ” ፍትህ ለመሀመድ! ” በማለት ፍትህ ርትዕን እየጠየቁለት ይገኛሉ !
ብላቴናው መሀመድ እርስዎ ካረፉበት ሆቴል የአንድ ኪሎ ሜትር ርቀት ካለው የዶር ፈቂ ሆስፒታል ተጋድሞ ይገኛል ፣ አስጎብኝዎ የሴቶች ማህበር ተብየዎችም ሆኑ የቆንስል ሰዎች ለምን ብላቴናው መሀመድን እንዲጎበኙ እንዳላደረጉ አልገባኝም … በተለይ እንደ ልጅ እናትነትዎ የታዳጊዎን አበሳ ፣ እንደ ሴትና እንደ ሴቶች ተወካይ ዳይሬክቶሬትነትዎ ሰብዕናዋን ለንዋይ ፍቅር ያልሸጠችውን እናት ሃሊማን ማግኘት በራሱ ለእርስዎ መታደል ነው … በሆስፒታል ሄደው ብላቴናው መሀመድንና የመሀመድን እናት ይጎብኙ ፣ በአልጋ ላይ ተንጋሎ ባደገው ህጻን የግፉን ልክ ፣ ከመሀመድ እናት ከሀሊማ ደግሞ ጽናትና የእምነት ጥንካሬን ይማራሉ ! የእናት የልጅና የቤተሰቡን የ9 ዓመት የመከራ ጉዞም ይረዱታል … ! እናም ብላቴናውን ይጎብኙት !
እደግመዋለሁ ብላቴናው መሀመድን ይጎበኙት ዘንድ አደራየ የጠበቀ ነው ፣ ሳውዲ ለምንም ይሁን ለምን ከመጡ አይቀር መሀመድን ጎብኝተው በነካ እጅዎ ስለበደሉ ለሳውዲ ከፍተኛ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሃላፊዎች አቤት ይበሉልን ! ለፍትህ አካላትና ለሚመለከታቸው ባለስልጣናት በብላቴናው መሀመድ አብድልአዚዝ የተፈጸመውን ተዳፍኖ የከረመ በደል ያቀርቡልን ፣ ” ፍትህ ለመሀመድ !” ብለው ይጠይቁን ዘንድ በባንዴራው ብቻ ሳይሆን በልጆችዎ እንማጸንዎታለን!