በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን፣ የሰሜን ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ በብፁዕ አቡነ ኤፍሬም የደብረ ብርሃን መኖርያ ቤታቸው፣ ታኅሣሥ 26 ቀን 2008 ዓ.ም. ምሽት ቦምብ መፈንዳቱ ተገለጸ፡፡
በመንበረ ጵጵስናው የሊቀ ጳጳሱ መኖርያ በሚገኘው ዕቃ ቤት አጠገብ የፈነዳው ቦምቡ፣ በብፁዕ አቡነ ኤፍሬምም ኾነ በሌላ ሰው ላይ ያደረሰው ጉዳት የለም፡፡
ከፍተኛ ድምፅ የተሰማበት የፍንዳታው ስፍራ ጉድጓድ ፈጥሮ የሚታይ ሲኾን የዕቃ ቤቱ መስኮቶች ረግፈዋል፤ በመንበረ ጵጵስናው አጠገብ በሚገኘው የሀገረ ስብከቱ ጽ/ቤት የሊቀ ጳጳሱ ቢሮ መስተዋቶችም ተሰነጣጥቀዋል፡፡
የከተማው ፖሊስ ጽ/ቤት፣ አምስት የሀገረ ስብከቱን ሓላፊዎች እና ሠራተኞች ታኅሣሥ 27 እና ጥር 3 ቀን በቁጥጥር አውሎ ምርመራ እያካሔደ መኾኑ ተጠቅሷል፡፡
የሰው ኃይል አስተዳደር ክፍል ሓላፊው ቀሲስ አስቻለው ፍቅረ፣ የሕግ ክፍሉ መምህር አክሊል ዳምጠው፣ ኹለት የጥበቃ ሠራተኞች እና አንድ የሊቀ ጳጳሱ የቅርብ ዘመድ በአስተዳደሩ ፍ/ቤት በተለያዩ ጊዜያት በፖሊስ ቀርበው ከ7 እስከ 10 ቀናት ጊዜ ቀጠሮ ተጠይቆባቸዋል፡፡
ፍንዳታው በተከሠተበት ወቅት፣ ብፁዕ አቡነ ኤፍሬም የልደትን በዓል ለማክበር በመርሐ ቤቴ እንደ ነበሩ የሀገረ ስብከቱ ምንጮች ተናግረዋል፡፡
ድርጊቱ “የማስፈራራት ዓላማ ያለው ነው፤” ያሉት ምንጮቹ፥ ከክሥተቱ ኹለት ሳምንት በፊት በሊቀ ጳጳሱ የዝውውር ርምጃ የተወሰደባቸው የአስተዳደር ክፍሉ ሓላፊና ሌሎች የጥቅም ግብረ አበሮቻቸው በብፁዕ ሊቀ ጳጳሱ እና በአስተዳደራቸው ላይ ጫና ለመፍጠር ያቀዱበት ሳይኾን እንደማይቀር ጠቁመዋል፡፡
በአስተዳደር ጉባኤ ታይቶ በሊቀ ጳጳሱ የጸደቀ ነው በተባለው ውሳኔ÷ በሙስና፣ በባለጉዳዮች እንግልት እና በጠንቋይ አስጠንቋይነት ክፉኛ የሚተቹት የሀገረ ስብከቱ የሰው ኃይል አስተዳደር ክፍል ሓላፊ ቀሲስ አስቻለው ፍቅረ ከደረጃቸው ዝቅ ተደርገው ወደ ስታቲስቲክስ ክፍል ባለሞያነት መዘዋወራቸው ታውቋል፡፡
በሙስና፣ በመልካም አስተዳደር ዕጦት፣ አስተምህሮንና ሥርዓትን በሚፃረሩ የኑፋቄ አካሔዶች ገዳማቱን በማተራመስ እና በጠንቋይ አስጠንቋዮች ሳቢያ ከወረዳ ቤተ ክህነት፣ ከአገልጋዮች እና ከምእመናን በርካታ ምሬቶች እና አቤቱታዎች ለብፁዕነታቸው እና ለጽ/ቤታቸው ሲቀርቡ የቆዩ ሲኾን ከሰላም አኳያም አፋጣኝ መፍትሔ እንዲፈለግላቸው የዞኑ አስተዳደር ለሀገረ ስብከቱ ጽ/ቤት ማሳሰቢያ ሲሰጥ መቆየቱ ተገልጧል፡፡
ጸሎተኛነታቸው እና በአባትነታቸው ተወዳጅ የኾኑት የዕድሜ ባዕለጸጋው ብፁዕ አቡነ ኤፍሬም፣ ሀገረ ስብከቱን በሊቀ ጳጳስነት ሲመሩ ከ፳ ዓመታት በላይ ማስቆጠራቸውን ያስረዱት ምንጮቹ፣ የተቃጣባቸው አደጋ፣ “በግል ጥቅም ኅሊናቸው ከታወረና ለመናፍቃን ውስጣዊ መዋቅራዊ ድጋፍ በመስጠት የቤተ ክርስቲያኒቱን ህልውና አሳልፎ ከመስጠት ወደ ኋላ ከማይሉ አካላት በቀር በሌላ በማንም ሊታሰብ አይችልም፤” በማለት በእጅጉ ማዘናቸውን ገልጸዋል፡፡
በሕገ ቤተ ክርስቲያኑና በቃለ ዐዋዲ ደንቡ መሠረት፣ የሀገረ ስብከት ዋና ጽ/ቤት በሀገረ ስብከቱ ለሚገኘው የቤተ ክርስቲያን አስተዳደር ከፍተኛ የሥራ አስፈጻሚ አካል ነው፡፡ በቅዱስ ሲኖዶስ የተሾመው ሊቀ ጳጳሱ፣ የሀገረ ስብከቱ ጽ/ቤት መሪና ተጠሪ ሲኾን ለአስተዳደሩም የበላይ ሓላፊ ነው፡፡ የሰው ኃይል ቅጥር፣ ዕድገት፣ የሥራ ዝውውር፣ ደመወዝ መጨመር እና ሠራተኛ ማሰናበት ሊፈጸምና በሥራ ላይ ሊውል የሚችለው በአስተዳደር ጉባኤው ታይቶ እና ተጠንቶ በሊቀ ጳጳሱ ጸድቆ መመሪያ ሲሰጥበት ነው፡፡
ምንጭ ሐራ ዘተዋሕዶ
↧
በሊቀ ጳጳሱ መኖርያ ቤት ቦምብ ፈነዳ ፤ አምስት የሀገረ ስብከቱ አላፊዎች እና ሠራተኞች ተጠርጥረዋል
↧