የ 7/8 ዓመት እና የቀናት ልዩነት
በኢትዮጵያና በአውሮፓ የዘመን አቆጣጠር መካከል የ7 ወይም 8 ዓመት ልዩነት ይታያል። ከጥር እስከ ጳጉሜ መጨረሻ የ8 ዓመት፣ ከመስከረም እስከ ታህሳስ መጨረሻ የ7 ዓመት ልዩነት አለ። የዚህ ልዩነት የተፈጠረው ክርስቶስ በተወለደበት ዘመን ላይ በነበረው የግምት አንድ አለመሆን ላይ ነው። እንደ አውሮፓ አቆጣጠር በመጪው ጥር የክርስቶስ ዕድሜ 2016 ነው። በኛ አቆጣጠር ደግሞ 2008 ይሆናል። የቅርብ ጊዜ ምርመራዎች ባሳዩት መሠረት በቀጣዩ ዓመት የክርስቶስ ዕድሜ 2023 ነው። ፈረንጆቹ በ7 ዓመት፣ እኛ ደግሞ በ15 ዓመት ተሳስተናል። ይኸው ነው።
በኢትዮጵያና በአውሮፓውያን የዘመን አቆጣጠር የቀናት ልዩነትም አለ። የኛ መስከረም 1 በነሱ ሴፕቴምበር 11 (በሠግር ዓመት 12 ይሆናል)። የዚህ የ10ቀን ልዩነት እንዴት መጣ? የልዩነቱ መነሻ ያለው በግሪጎሪያዊና በጁሊያን አቆጣጠር ውስጥ ነው።
በፀሐይ አቆጣጠር አንድ ዓመት 365 ዕለት፣ 5 ሰዓት፣ 48 ደቂቃ እና 46 ሰከንድ ነው። ይህ በጁሊያን ካላንደር ወደ 365 ዕለት፣ ከ 6 ሰዓት (ሩብ ዕለት ወይም የዕለት አንድ አራተኛ) ተጠጋጋ። በዚህ መሠረት 3 ዓመቶች 365 ዕለት ይኖራቸውና አራተኛው ዓመት 366 ዕለት ይኖሩታል። አራቱ ሩብ ዕለት በአራት ዓመት አንድ ዕለት ይሆናሉ። ይህን አንድ ዕለት ፈረንጆቹ 28 የነበረውን ፌብሯሪ 29 ያደርጉታል። እኛ ደግሞ ለሦስት ተከታታይ ዓመታት 5 የሆነችውን ጳጉሜ 6 እናደርጋታለን።
5 ሰዓት፣ 48 ደቂቃ፣ 46 ሰከንድ ወደ 6 ሰዓት ሲሸጋሸግ 11 ደቂቃ፣ 14 ሰከንድ በትርፍ ተጨምሯል። ይኸ በ400 ዓመት ውስጥ አነሰ ቢባል የ3 ዕለት ትርፍ ያስከትላል። ከዚህ በመነሳት እ.ኤ.አ. በ1582 በአባ ጎርጎሪዮስ አማካይነት ማስተካከያ ተደረገ። ከ325ቱ የኒቂያ ጉባኤ እስከ 1582 ባለው የ 1, 257 ዓመት ውስጥ የ10 ዕለት ትርፍ እንዳለ ተሰላ። ኦክቶበር 5፣ 1582 ላይ 10 ዕለቱ ተጨምረው ያ ዕለት ኦክቶበር 15፣ 1582 ተባለ። ያን ዕለት በኛ አቆጣጠር ጥቅምት 8፣ 1575 ነበር። በዚያ ዕለት የ7ቀን ልዩነት ተፈጠረ።
አሁን ግን ልዩነቱ የ10 ቀናት ነው። ይህ ደግሞ እንዴት እንደሆነ እንይ። የጎርጎሮሳውያኑ የዘመን አቆጣጠር ከጁሊያን እንደተለየ ላለፉት የ1,257 ዓመታት የ10 ቀናት ተረፉን ካስተካከለ በኋላ ለመጪዎቹም ዘመናት የ11 ደቂቃዎች እና የ14 ሰከንዱን የትርፍ ጊዜ ማስተካከያ ቀመርም አስቀመጠ።
ቀመሩ በ400 ዓመት ውስጥ ሦስት ጊዜ የሦስት ዕለት ጭማሪ (በሊፕ ዪር ወይም ሠግር) እንዳይደረግ ያቅባል። ፌብሯሪ 29 የሚሆነው ለ 4 ሲካፈሉ ቀሪያቸው ዜሮ በሚሆኑ ዘመኖች ነው። ዘመናቱ በ100 ቤት በሆኑ ጊዜ ግን ለ400 ተካፍለው ቀሪ ዜሮ ባላቸው ብቻ ፌብሯሪ 29 ይሆናል።
በዚህ መሠረት በ1600 ዓ.ም ለ400 ተካፍሎ ቀሪው ዜሮ ስለሆነ በዚያ ዓመት ፌብሯሪ 29 ሆኗል። በ1700፣ በ1800፣ እና በ1900 ግን በነዚያ ዓመታት ፌብሯሪ 29 መሆን ሲገባው ተዘሎ 28 ሆኗል። በመደበኛው አደማመር 1700, 1800, እና 1900 ለ4 ተካፍለው ቀሪው ዜሮ ስለሆነ ፌብሯሪ 29 ይሆን ነበር። በአዲሱ ሕግ ግን እነዚህ ለ400 ሲካፈሉ ቀሪው ዜሮ ስለአልሆነ ፌብሯሪ በ28 ቀጥሏል። በነዚህ ሦስት ዓመታት የተቀነሱት 3 ዕለታት በፊት 7 ዕለት የነበረውን የኛን እና የነርሱን ልዩነት ወደ 10 ዕለት ከፍ አድርጎታል። የዘመን ቆጠራ ልዩነታችን በአጭሩ ይኼ ነው።
ከጁሊያን የዘመን አቆጣጠር ጋር የተቀራረበውን የኛን የዘመን አቆጣጠር በጎርጎሮሳውያን መሠረት አስተካክለነው ቢሆን ኖሮ የሚከተለውን ይኖረን ነበር። ጥቅምት 8፣ 1575 የአስር ዕለቱ ማስተካከያ ሲደረግ የኛ ቀን በዚያ ዕለት ጥቅምት 18፣ 1575 ይሆን ነበር። ከዚያ በኋላ ደግሞ በ1700, በ1800, እና በ1900 ላይ 6 ልትሆን የሚገባት ጳጉሜ በ5 ትቆጠራለች። እንደዚያ መጥተን ቢሆን ኖሮ የአውሮፓውያኑ ሴፕቴምበር 1 እና የኛ መስከረም 1 አንድ ቀን ባይውልም ይቀራረብ ነበር።
ጳጕሜ 7 ልትሆን ትችላለችን?
በኢትዮጵያውያን የዘመን አቆጣጠር መሠረት በአንድ በኩል በየ300 ዓመቱ በሌላ በኩል ደግሞ በየ600 ዓመቱ አንድ ጊዜ ጳጉሜ 7 ልትሆን ትችላለች የሚል ትወራዊ አስተያየት አለ። በዚህ ላይ የራሴን ሐሳብ እሰነዝራለሁ። ሐሳቡን በደፈናው ከመቃወምና ከመደገፍ ይልቅ የውይይት ነጥቦች ማዋጣት ይሻላል።
በየዓመቱ ያለ አግባብ እየተጨመረ ሲቆጠር የሚኖር የ11 ደቂቃና የ14 ሰከንድ ትርፍ አለ። ይህ ጊዜ አሁን በተጠጋጋ ስሌት በ400 ዓመት ውስጥ አነሰ ቢባል የ3 ዕለት ልዩነት ያመጣል። [በመቶ ዓመት የሦስት ሩብ ዕለት በሁለት መቶ ዓመት የአንድ ዕለት ተኩል ትርፍ ነው።] ይህን ለማስተካከል በ400 ዓመት ውስጥ የ3 ዕለት ቅናሽ ይደረጋል። ይኸ ማለት በ400 ዓመት ውስጥ ጳጉሜ 6 መሆን ይገባት ከነበረው ውስጥ ሦስት ጊዜ በ5 ትቀጥላለች። በዚህ አካሔድ ጳጉሜ በሠግር ዓመት (ሊፕ ዪር) 6 የማትሆንበት ዓመት አለ፤ ወይም ደግሞ 5 የምትሆንበት ዓመት አለ ይባላል እንጂ እንዴት በየ300 ዓመቱ ጳጉሜ 7 ትሆናለች ይባላል? [በየ600 ዓመት የሚለው ሐሳብ አሳማኝ መነሻ ስላለው እሱን ወደ ኋላ እመጣበታለሁ።]
ሦስቱ ትርፍ ዕለት በ400 ዓመት አንዴ ይቀነስም ከተባለ የምናገኘው ውጤት እንደሚከተለው ነው። ቅናሹ ጳጉሜ 6 በምትውልበት በሉቃስ ዓመት ከሆነ ያኔ ጳጉሜ 3 ትሆናለች። ያለበለዚያ ጳጉሜ 5 በምትውልበት ዓመት ከሆነ ያኔ ጳጉሜ 2 ትሆናለች። በየ300 ዓመቱ ጳጉሜ 7 ልትሆን ትችላለች ማለት ግን ግራ ያጋባል።
ተጨማሪ ንፅፅር እና ማብራርያ
በአንድ ዓመት ውስጥ 365 ዕለት፣ 5 ሰዓት፣ 48 ደቂቃ እና 46 ሰከንድ እንዳለ አይተናል። ከ365 ውጭ ያለው ጊዜ ምን ያህል ዕለት ነው ካልን 0.2421991 ዕለት ነው። ይህ ከሩብ ዕለት (ከ0.25) በትንሹ አነስ ይላል። በአራት ዓመት ውስጥ ሲሰበሰብ አንድ ዕለት በቅጡ አይሞላም። ጥቂት ይቀረዋል። 0.2421991 ሲበዛ 4 የሚሆነው 0.9697964 ነው። ተረፉ በ400 ዓመት የሚሆነው ደግሞ 96.97964 ዕለት ነው።
ይህ ማለት 96 ዕለት፣ ከ21 ሰዓት፣ ከ6 ደቂቃ፣ ከ40 ሰከንድ ነው። 97 ዕለት ለመሙላት 2 ሰዓት፣ 53 ደቂቃ እና 20 ሰከንድ ይቀረዋል። መቶ ዕለት ለመሙላት ደግሞ 3 ዕለት፣ 2 ሰዓት፣ 53 ደቂቃ እና 20 ሰከንድ ያስፈልገዋል።
የጁሊያን የዘመን አቆጣጠር መጠነኛ ማጠጋጋት ያደርግና የዓመቱን ጊዜ 365 ከ 0.25 ዕለት ያደርገዋል። ይህ በሌላ አገላለጽ 365 ¼ ኛ ዕለት ይሆናል። የጁሊያን የዘመን አቆጣጠር ትርፉን ዕለት የሀያ አራት ሰዓት አንድ አራተኛ ያደርገውና 6 ሰዓት ይሆናል። አሁንም በሌላ አገላለጽ፣ በጁሊያን አካሔድ አንድ ዓመት 365 ከ25/100ኛ ዕለት ነው። በጁሊያን አካሔድ ትርፉ ሩብ ዕለት በ 4 ዓመት አንድ ሙሉ ዕለት ይሆናል። በ400 ዓመት ደግሞ 100 ዕለት ይወጣዋል።
የጁሊያን የዘመን አቆጣጠር በ400 ዓመት ውስጥ የ74 ሰዓት፣ የ53 ደቂቃ እና የ20 ሰከንድ ትርፍ ያመጣል። በሌላ አገላለጽ በ400 ዓመት ውስጥ 3 ዕለት፣ 2 ሰዓት፣ 53 ደቂቃ እና 20 ሰከንድ ስህተት ያሣያል።
የግሪጎሪያን የዘመን አቆጣጠር አንድ ዓመትን 365 ከ 97/100ኛ ዕለት ያደርገዋል። ተረፉ 97/100ኛ ወይም 0.2425 ዕለት ነው። ይህ ተረፍ በአራት ዓመት ውስጥ 0.9690 ዕለት ስለሚሆን አንድ ሙሉ ዕለት አይሞላም። ተረፉ በ400 ዓመት ደግሞ (400 X 0.2425) 97 ዕለት ይሆናል። ይኸ የ97 ዕለት ተረፍ ቀጥተኛ ከሆነው ከ 96.87764 ዕለት ጋራ የተቀራረበ ነው። ጥቂት ጭማሪ ግን አድርጓል። ይህም 2 ሰዓት፣ ከ53 ደቂቃ ከ 20 ሰከንድ ነው። እንዲህም ሆኖ ታዲያ በ400 ዓመት የ 3 ዕለት፣ ከ 2 ሰዓት፣ ከ 53 ደቂቃ፣ ከ 20 ሰከንድ ስህተት ከሚያሳየው ከጁሊያን የዘመን አቆጣጠር አካሔድ የተሻለ ነው።
ከጁሊያን ስሌት ይልቅ የግሪጎሪያን ወደ ትክክለኛ አቆጣጠር ይቀርባል። ከግሪጎሪያን የበለጠ ደግሞ ወደ ትክክለኛው የሚቀርብ ስሌት አለ። ይህ ስሌት የተቀመረው ዑመር ኻያም በተባለው የሥነፈለክ ሊቅ ነው። በዑመር ኻያም ስሌት አንድ ዓመት 365 እና 8/33ኛ ዕለት ይሆናል። የ8/33ኛ ዕለት ተረፍ በሌላ አገላለፅ 0.242424 ነው። ይህ ተረፍ በ400 ዓመት ውስጥ 96.9696 ዕለት ይሆናል። ይህም ቢሆን ከግሪጎርያን የበለጠ ለፍፁምነት ይቀርባል እንጂ ጉድለት ያሣያል።
ጳጕሜ 7 ልትሆን ትችላለች!
በአንድ ዓመት ውስጥ ያለው 365 ዕለት፣ 5 ሰዓት፣ 48 ደቂቃ እና 46 ሰከንድ ነው። ከ365 ዕለት የተረፈው 5 ሰዓት፣ 48 ደቂቃ እና 46 ሰከንድ 6 ሰዓት ለመሙላት 11 ደቂቃ እና 14 ሰከንድ ይቀረዋል። ሆኖም ለአሠራር እንዲቀል ተብሎ ወደ 6 ሰዓት ተጠግቷል። 365 ዕለታት ለ12 ወራት ሲካፈል ለሁሉም 30 ዕለት ይደርሰውና 5 ዕለት ይተርፋል። ይኸ 5 ዕለት 13ኛው ወር ጳጉሜ ተብሎ እዚያው ተመድቧል። ከየዓመቱ ደግሞ በማጠጋጋት የሚተርፈው 6 ሰዓት በ4 ዓመት 24 ሰዓት ይሆናል። 24 ሰዓት አንድ ዕለት በመሆኑ ይኸ በ4 ዓመት ተጠራቅሞ የሚገኝ ዕለት በ4 ዓመት አንዴ ጳጉሜ ላይ ይጨመራል። ስለዚህ ጳጉሜ ለሦስት ተከታታይ ዓመታት 5 ትሆን እና በ4ኛው ዓመት 6 ትሆናለች።
ይህን ምሳሌ እንይ።
ጳጉሜ 6 የምትሆነው ሁሌም በሉቃስ ዘመን ነው። ወይም ደግሞ ዓመቱን ለ4 አካፍለን ቀሪው ሦስት በሆነበት ዘመን ጳጉሜን 6 እናደርጋለን። ለምሳሌ ዘንድሮ 2007 ለ 4 ሲካፈል ቀሪው ሦስት በመሆኑ የ2007 ጳጉሜ 6 ነች። በሌላ አነጋገር ሁሌም ወደ ዮሐንስ ዘመን ስንሸጋገር ከርሱ ቀድሞ ያለው የሉቃስ ዘመን ጳጉሜን 6 ያደርገዋል። የዮሐንስ ዘመንም ከሌሎቹ በተለየ አንድ ቀን ዘግይቶ ይገባል ወይም ይጀምራል። በየዓመቱ ከ365 ላይ ትርፍ ሆኖ የሚገኘው 5 ሰዓት፣ 48 ደቂቃ እና 46 ሰከንድ በ4 ዓመት ሲጠቃለል የሚሆነው 23 ሰዓት፣ 15 ደቂቃ እና 4 ሰከንድ ነው። ይኸ አሁንም 24 ሰዓት አይሞላም። ስለዚህ አንድ ሙሉ ዕለት አይደለም። አንድ ዕለት ለመሙላት የ44 ደቂቃ እና የ56 ሰከንድ ጉድለት ያሣያል።
በዓመት የ5 ሰዓት፣ የ48 ደቂቃ እና የ48 ሰከንድ የሆነው ትርፍ በ 400 ዓመት ሲሰበሰብ 96 ዕለት፣ 21 ሰዓት፣ 46 ደቂቃ እና 40 ሰከንድ ይወጣዋል። በጁሊያን ቆጠራ በየ4 ዓመቱ አንድ ዕለት ስለሚጨመር፣በ400 ዓመት የሚጨመረው 100 ዕለት ነው። ትክክለኛው ጭማሪ ግን በ400 ዓመት 96 ዕለት፣ 21 ሰዓት፣ 46 ደቂቃ፣ እና 40 ሰከንድ ነው። ይኸ 100 ዓመት ለመሙላት 3 ዕለት፣ 2 ሰዓት፣ 53 ደቂቃ እና 20 ሰከንድ ይቀረዋል። ስለዚህ በ400 ዓመት ውስጥ በትንሹ የ3 ዕለት ትርፍ ይፈጠራል።
የጎርጎርዮስ አቆጣጠር ያስተካከለው ይህንን ነው። የጁሊያን አቆጣጠር በየ4 ዓመቱ አንድ ዕለት ፌብሯሪ ላይ ይጨምራል። ይኸ በ400 ዓመት 100 ዕለት ይሆናል። የጎርጎርዮስ አቆጣጠር ግን በ400 ዓመት ውስጥ 97 ዕለት ብቻ እንዲጨመር አደረገ። በሌላ አገላለፅ በየ400 ዓመቱ የሦስት ዕለት ቅናሽ አደረገ።
ቅናሹ የተደረገው እንደሚከተለው ነው። በመቶ ብዜት በሚገኙ ዓመተ ምሕረቶች ለ400 ተካፍለው ቀሪው ዜሮ ከሆነ በዚያ ዓመት ፌብሯሪ በመደበኛው አካሔድ መሠረት 29 ይሆናል። አንድ ዕለት ይጨመርለታል። ቀሪው ዜሮ ካልሆነ ግን በዚያ ዓመት ፌብሯሪ የሚደረግለት ጭማሪ ይቀርና በ28 ይፀናል። በዚህ አካሔድ በ400 ዓመት ውስጥ የ3 ዕለት ቅናሹ ይከናወናል።
የኢትዮጵያ የዘመን አቆጣጠርም አንዱን የፀሐይ ዓመት የሚወስደው በተጠጋጋ ስሌት 365 ዕለት ከ 6 ሰዓት አድርጎ ነው። የ 6 ሰዓቱ ተረፍ በ 4 ዓመት 24 ሰዓት ወይም አንድ ዕለት ይሆናል። ይህ ዕለት ጳጉሜን በ4 ዓመት አንዴ 6 ያደርጋታል። (ይቀጥላል)
ምንጭ አዲስ አድማስ ፀሀፊ በአብነት ስሜ