በትግራይ ክልል ዓደዋ ከተማ ተወልደው በዚያው የአንደኛ ደረጃ ትምህርታቸውን በንግሥተ ሳባና በዓዲግራት አግአዚ፣ በኋላም በኮተቤ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ሁለተኛ ደረጃ ቀጥለዋል። በ1951 ዓ.ም.
በሐረር (በቀድሞ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ) የጦር አካዳሚ ለሦስት ዓመታት ከተማሩ በኋላ፣ በክብር ዘበኛ የጦር ክፍል ተመድበው ሠርተዋል፡፡ በንጉሡ ዘመን በአሜሪካ ከፍተኛ ወታደራዊ ትምህርት ከተከታተሉ በኋላ፣ በቀድሞው ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ የሕግ ትምህርት በመከታተል ላይ ሳሉ አብዮቱ ፈነዳ። ለውጡን ተከትሎ የደርግ አባል፣ እንዲሁም የኢሕዲሪ ምክትል ፕሬዚዳንት ሆነው በደርግ ሥርዓት በከፍተኛ ሥልጣን አገልግለዋል። የደርግ ሥርዓት በ1983 ዓ.ም. ከተገረሰሰ በኋላ ከጓደኞቻቸው ጋር ክስ ተመሥርቶባቸው ለ20 ዓመታት በእስራት ላይ ከቆዩ በኋላ በምሕረት ከተፈቱት የደርግ ከፍተኛ ባለሥልጣናት መካከል አንዱ ናቸው፡፡ በቅርቡ የታተመውን “እኛና አብዮቱ” የተባለውን መጽሐፋቸውን ተንተርሶ የማነ ናግሽ ተያያዥ ርዕሰ ጉዳዮች በማንሳት ከሌተና ኮሎኔል ፍሰሐ ደስታ ጋር ቆይታ አድርጓል።
ሪፖርተር፡- አብዮቱ ሲፈነዳ የእርስዎ ድርሻና እንቅስቃሴ ምን ይመስል ነበር?
ሌ/ኮ ፍሰሐ፡- በመሠረቱ በወቅቱ የዩኒቨርሲቲ ተማሪ እያለሁ የሕግ ተማሪ ስለነበርኩ፣ “ትምህርታችሁን ብቻ ተከታተሉ እንጂ ፖለቲካ ውስጥ እንዳትገቡ፤” ተብለን ተከልክለናል፡፡ ስለሆነም የሚደረገውን ከማየትና ከማዳመጥ ባለፈ የጎላ ተሳትፎ አልነበረኝም፡፡ ክትትልም ነበር፡፡ አልፎ አልፎ ግን እንቅስቃሴውን ለማየት ከትምህርት ቤት እየወጣሁ ክቡር ዘበኛ መኮንኖች ክበብም እየሄድኩ ጓደኞቼ የሚሉትን በማዳመጥ ምን ይደረግ እንደነበር ሁኔታዎችን እገመግም ነበር፡፡ ከዚህ ውጪ ግን “አክቲቭ” ሚና ለመጫወት በጣም አስቸጋሪ ነበር፡፡ ውስጥ ለውስጥ ግን ከአንዳንድ ወታደሮችና መኮንኖች ጋር እንገናኝ ነበር፡፡ ስለዚህ ያ ሥርዓት መለወጥ እንደነበረበት የሁላችንም ዕምነት ነበር፡፡ ከዚህ ባለፈ ይኼ ነው የሚባል ጉልህ ሚና አልነበረኝም። እንደ ማንኛውም ወጣት ግን ፀረ ፊውዳል ነበርኩ፡፡
ሪፖርተር፡- በእንቅስቃሴው ውስጥ ጉልህ ተሳትፎ ካልነበረዎት እንዴት ኋላ ላይ በአራተኛ ክፍለ ጦር የደርግ አባል አባል ሆነው ሊመረጡ ቻሉ?
ሌ/ኮ ፍሰሐ፡- እንግዲህ የወታደሮች አዛዥ ነበርኩ፡፡ በእኔ ላይ ዕምነት ነበራቸው፡፡ በማስተምራቸው፣ እንዲሁም ደግሞ በራሳቸው ሁኔታ በማደርግላቸው አመራር ስለሚደሰቱ ያን ጊዜ ስለወደዱኝ ነው የመረጡኝ፡፡ እንዲያውም አልሄድም ብዬ ነበር። “ትክክል አይደለህም” ብለው ስላስገደዱኝ ነው የሄድኩት፡፡ ያኔ የአብዮቱ አቅጣጫ ወዴት እንደሆነ አይታወቅም ነበር፡፡ ኃላፊነት ሲሰጡኝ ግን እምቢ ማለት አልችልም፡፡ ወቅቱም አስቸጋሪ ስለነበር የእኔ መግባት አንዳንድ ነገሮችን ሊያቃልል ይችላል በሚል ዕምነት ነው የገባሁት፡፡
ሪፖርተር፡- አብዮቱም ፈነዳ፣ ያ ሁሉ ታለፈ፡፡ ዛሬ ሦስተኛ መንግሥት ላይ ሆነው ዞር ብለው ሲመለከቱት የንጉሡን ሥርዓት እንዴት ነው የሚያስታውሱት? ማሻሻያ አድርጎ ቢሆን…
ሌ/ኮ ፍሰሐ፡- እንግዲህ ሥርዓቱ የታወቀ ነው፣ ፊውዳል ነው፡፡ የጃንሆይ ፊውዳል ሥርዓት ደግሞ በዓለም ከነበሩት ይቅርና ከአካባቢያችን፣ ከአፍሪካም ሆነ ከጎረቤቶቻችንም እኩል መራመድ አልቻለም፡፡ የመሬት ሥርዓቱ፣ የሕዝቡ ኋላቀርነት፣ የመኃይምነቱ ደረጃ ሲታይ ሥርዓቱ የራሱ የሆነ ድክመት ነበረው፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ንጉሡ የራሳቸው የሆነ ጥንካሬ ነበራቸው፡፡ በዓለም አቀፍ ደረጃ፣ በአሜሪካ አኅጉር የነበራቸው ተሰሚነት ከፍተኛ ነበር፡፡ በውስጥ የነበረው የኢኮኖሚው ሁኔታ፣ የመሬት ይዞታው፣ ወዘተ ሲታይ ሕዝቡ በዚህ ዓይነት ሥርዓት ተተብትቦ ነበር የተያዘው ማለት ይቻላል፡፡ እናም አሁን ላይ ሆኜ ስመለከተው ጠንካራም ደካማም ጎን ነበረው፡፡ እነዚያ ደካማ ጎኖችን በወቅቱ ማሻሻል አልተቻለም፡፡ ንጉሡ ደግሞ ፍፁማዊ ነበሩ፡፡ በአጠቃላይ ሥርዓቱ በእሳቸው ሥር ከሚሆን ሕገ መንግሥታዊ ቢሆን ኑሮ ቀጣይነት ይኖረው ነበር፡፡ ነገር ግን ይኼ ሁሉ በወቅቱ አልተደረገም፡፡ ያመለጣቸው ዕድል ነው፡፡ ወቅቱ ደግሞ የሶሻሊዝም እንቅስቃሴ በዓለም አቀፍ ደረጃ የተቀጣጠለበት ነበር፡፡ ስለዚህ
ወጣቱና ተራማጅ ኃይሉ ሶሻሊዝምን ለማስፈን ጉጉት ስለነበረው የፊውዳል ሥርዓቱ ለመቆየት ዕድል አልነበረውም፡፡
ሪፖርተር፡- በወቅቱ ያራመዳችሁት የፖለቲካ ፍልስፍና አሁንም ትክክል ነበር በሚለው አቋምዎ መፅናትዎን በመጽሐፍዎ የተመለከትኩ መሰለኝ፡፡ አቋምዎን አልቀየሩም? የሶሾሊዝም ርዕዮተ ዓለም ክፍተቱ አተገባበሩ ላይ ነው ብለው የሚያምኑት?
ሌ/ኮ ፍሰሐ፡- በመሠረቱ ሶሻሊዝም በርዕዮቱ ዓለም መሠረቱ ትክክል ነው፡፡ ጥሩም ሥርዓት ነው፡፡ ለታችኛው ለሚበዘበዘው የኅብረተሰብ ክፍል የቆመ ሥርዓት ነው፡፡ አካሄዱ ላይ ግን ማርክስ የካፒታሊዝም ሥርዓት ሲበሰብስ የሚቀጥል ሥርዓት ነው ብሎ ነበር። በኋላ ሌኒን ኋላቀር አገሮች በአጭር መንገድ ባደጉ ሶሻሊስት አገሮች ድጋፍ በአቋራጭ በብሔራዊ ዴሞክራሲያዊ አካሄድ ግባቸውን ሊመቱ ይችላሉ የሚል ይዞ መጣ፡፡ ይኼ ከብዙ ነገሮች አንፃር ደካማ ጎን ነበረው፡፡ ሁለተኛ ሶሻሊዝም በአንድ ኅብረተሰብ ከመጀመሪያው ለመነሳት በመደራጀትና በብዙ መንገድ እኩልነት ለማስፈን በመሞከሩ ብዙ ጥሩ ገጽታዎች አሉት፡፡ ከዚያ በኋላ ሰዎች የሶሻሊዝም ሥርዓትን መጠቀሚያ እያደረጉት ሲሄዱ ነው ነገሮች የተበላሹት። ግለሰቦች በሚመስላቸው እየተረጎሙት ሄዱና የራሳቸው ሥልጣን ማደላደያ በሆነበት ጊዜ ሁኔታው እየተበላሸ ሥርዓቱ ፈሩን እየለቀቀ ሄደ፡፡ ነገር ግን ዴሞክራሲያዊ ገጽታው ደግሞ በጣም የላላ ነው፡፡ በዚህ በኩል ዴሞክራሲና ሶሻሊዝምን ማጣጣም አልተቻለም፡፡ የፓርቲው የውስጥ ዴሞክራሲ ብቻ ሳይሆን፣ ኅብረተሰቡም ውስጥ ዴሞክራሲ እንዴት ማጣጣም እንዳለበት ትልቅ የርዕዮተ ዓለም ግምገማ ማድረግ ይጠይቃል። ቢቻል እንደምለው ሶሻል ዴሞክራሲ የሚባለው ሥርዓት ብዙ ጠቀሜታ አለው፡፡ በአንድ በኩል ኅብረተሰቡን የሚያሳትፍና በእኩልነት የሚያይ ሆኖ፣ በሌላ በኩል ደግሞ የሕግ የበላይነትንና ዴሞክራሲን ስለሚያስፍን ተመራጭ ነው፡፡ ስዊድንና ብዙ አገሮች ይጠቀሙበታል፡፡ ለምሳሌ እንደ ስዊድን ያሉ የስካንዲቬኒያ አገሮችም ይጠቀሙበታል፡፡
ሪፖርተር፡- ወደ ዋናው የመጽሐፍዎ ይዘት ልመልስዎት፡፡ ከ20 ዓመታት በላይ በእስር አሳልፈው በምሕረት ከወጡ በኋላ ይህንን መጽሐፍ ለማዘጋጀት ያነሳሳዎት ምንድነው?
በርዕሰ ጉዳዩ ላይ ሌሎችም የደርግ ባለሥልጣናት ጽፈዋልና የተለየ ዕይታ ወይስ የተለየ መረጃ ስላለዎት ይሆን?
ሌ/ኮ ፍሰሐ፡- በመሠረቱ ያለፍንበትን ሁኔታ፣ ድክመታችንንና ጥንካሬያችንን የአሁኑ ወጣት ትውልድ እንዲያውቀውና እንዲማርበት እፈልጋለሁ፡፡ ስለዚህ በሥርዓቱ ውስጥ ግንባር ቀደም ሚና ስለነበረኝ የግድ ይህንን የማውቀውን ታሪክ ለዚህ ትውልድ አስረክቤ መሄድ አለብኝ ከሚል ነው፡፡ ሁለተኛው ራዕይ ያኔ የነበረው ትውልድ በወጣትነት ዕድሜው ብዙ ስህተቶች ተፈጽሟልና ይቅርታ ተባብለን ለዚህች አገር በአንድ ራዕይ፣ በአንድ አመለካከትና ቀና በሆነ መንፈስ ብሔራዊ ዕርቅ ሰፍኖ አገሪቷን ወደ ተሻለ ሁኔታ ለማድረስ የሁላችንም ድርሻ አለ ብዬ ስለማምን ነው፡፡
ሪፖርተር፡- እስካሁን በደርግ ከፍተኛ ባለሥልጣናት [የፕሬዚዳንት መንግሥቱ ኃይለ ማርያምና የሻምበል ፍቅረ ሥላሴ ወግደረስን ጨምሮ] ከወጡ ሥራዎች በይፋ በይቅርታ የሚጀምረው መጽሐፍ የእርስዎ ብቻ ነው፡፡ በመጽሐፉ ምርቃት ላይም ብዙ ሰዎችን ያስደሰተ እንደነበር ታይቷል። በዚያ ወቅትም፣ በሌሎች ተመሳሳይ መድረኮችም፣ በተለይ በኢሕአፓና በመኢሶን ደጋፊዎች መካከል አሁንም የማይታረቁ የሚመስሉ ጭቅጭቆች ሲደረጉ አስተውላለሁ፡፡ መፀፀትና ይቅርታ መጠየቅን ያቀዘቅዙት ይሆን?
ሌ/ኮ ፍሰሐ፡- በአጠቃላይ በጎ ነገሮች እንደነበሩ ሁሉ ጥፋቶችም ነበሩ፡፡ ለእነዚህ ጥፋቶች ይቅርታ መጠየቅ ተገቢ ነው ብዬ ነው የማምነው፡፡ ይቅርታው በእኔ ብቻ መቆም የለበትም፡፡ ሌሎች ድርጅቶችም ስህተት ሠርተው ከሆነ ስህተታቸውን ማመን አለባቸው። እኔ አንድ ቦታ ላይ መጀመር አለበት ብዬ ስላመንኩ ነው ይህንን ደፍሬ ያደረግኩት፡፡ አንዳንድ ሰዎች ላይወዱት ይችላሉ፡፡ “ለምንድነው ይቅርታ የምንጠይቀው? ምን አጠፋን?” ይሉ ይሆናል፡፡ የእነሱ መውደድና አለመውደድ የእኔ ጥያቄ አይደለም፡፡ የእኔ ጥያቄ ግን የማምንበት ነው፡፡ አላጠፋንም ማለት አንችልም፡፡ ማንም በዚያ ውስጥ ያለፈ የፖለቲካ ድርጅት «አላጠፋሁም» ካለ ዋና ውስጥ ገብቶ ውኃ አልነካኝም እንደማለት ነው። እርግጥ ነው አክራሪነት ዛሬም ይኖራል፡፡
አንዳንድ ያኔ የነበሩ የፖለቲካ ድርጅቶች ብዙ አክርረው ሲሟገቱ ይታያሉ፡፡ ግን እስከ መቼ ነው ይህ የሚቀጥለው? አንድ ቦታ ላይ ቆም ብሎ ማሰብ አይቻልም ወይ? አንድ ቦታ ላይ ቆም ብሎ ይቅር መባባል አይቻልም ወይ? ለወጣቱ ትውልድ ይህንን የጥላቻና የቂም በቀል መንፈስ አውርሰን ነው ወይ የምንሄደው? ስለዚህ የእኔ ዕምነት ወጣቱ ትውልድ የእኛን የቂም በቀል መውረስ የለበትም፡፡ ይቅር መባባልም መልመድ ካለብን እኛ ነን ማስተማር ያለብን፡፡ እርግጥ ነው ትናንት ሁላችንም በጠመንጃ አፈሙዝ ተናቁረናል፡፡ ዛሬ ጊዜው ተለውጧል፡፡ ሁኔታው ተለውጧል፡፡ በዚያ በ1960ዎችና በ1970ዎች አስተሳሰብ መሄድ ትክክል አይደለም፡፡ ዓለም ጥሎን እየሄድ ነው፡፡ ትናንት በደቡብ አፍሪካ ነጮች ያን ሁሉ ድርጊት ፈጽመው እንኳ ብሔራዊ ዕርቅ ሲያደርጉ እኛ ገና ንትርክ ላይ ነው ያለነው፡፡ ይኼ መቆም አለበት፡፡ እያንዳንዱ የፖለቲካ ድርጅትም ይቅር ብሎ ለብሔራዊ ዕርቅ መዘጋጀት አለበት፡፡
ሪፖርተር፡- ብሔራዊ ዕርቅን በመጽሐፍዎም አንስተውታል፡፡ የሥልጣን መጋራት ጥያቄ ይኖርበት ይሆን?
ሌ/ኮ ፍሰሐ፡- እኔ ስለብሔራዊ ዕርቅ ሳወራ የሥልጣን ጥያቄ የለበትም፡፡ ለሥልጣን ጥያቄ ሕገ መንግሥቱ አለ፡፡ በእሱ መሠረት ሁሉም በዚያው ይደራጅ፡፡ እኔ ብሔራዊ ዕርቅ የምለው “የተቃባነው ደም መድረቅ አለበት” ከሚል መነሻ ነው። አንድ ቦታ ላይ መቆም አለበት፡፡ ለአንዱ ሐውልት ተሠርቶ ለአንዱ የሚቀርበት ምክንያት የለም፡፡ ዛሬ ለቀይ ሽብር ከሠራህ፣ በነጭ ሽብርም እናቶች እኮ ያለቅሳሉ፡፡ ደርግ እንዳጠፋው ሁሉ ኢሕአፓም፣ ሌሎችም ያጠፉት የለም ማለት አይቻልም፡፡ በዚያን ጊዜ በቅለው የነበሩት የፖለቲካ ድርጅቶች ሁሉ ብዙ ጥፋቶች ሠርተዋል፡፡ ብዙ ጥፋት ተሠርቷል፡፡ ይቅር መባባልና ወደ ብሔራዊ ዕርቅ መሻገር አለብን፡፡ አለበለዚያ በቂም በቀል አንዱ ውጭ ሆኖ ሌላ ነገር ሲያወራ፣ ሌላው አገሩ ውስጥ ሆኖ ሌላ ነገር ሲያወራ ይህች አገር ወዴት ነው የምታመራው? ወጣቱ ትውልዱስ ምን ይማራል ከዚህ? ከእኛ መማር ያለበት ይቅር መባባልን፣ በሐሳብ መግባባትን፣ መቻቻልን፣ በጠረጴዛ ዙሪያ ቁጭ ብሎ ልዩነቱን መፍታት መቻልን ነው፡፡
ሪፖርተር፡- ይኼ የመፀፀት ስሜት ከመቼ ጀምሮ ነው የተሰማዎት? እስር ቤት ውስጥ እያሉ ወይስ ከተፈቱ በኋላ?
ሌ/ኮ ፍሰሐ፡- እስር ቤት ስገባና በኋላ እስር ቤት ቆይቼ ስወጣ የነበረውን ሁኔታ በሙሉ ተረዳሁ። ብዙዎቹን አገኘኋቸው፡፡ የተሠራውንም ነገር ለማየት ሞከርኩ፡፡ ከእያንዳንዱ ሰው ጋር እነጋገራለሁ፡፡ ይህን ሁሉ ፈትሼ ሳየው በጎ ነገርም ጥፋትም ነበር ብዬ አመንኩ፡፡ ለዚያ ጥፋት ይቅርታ መጠየቅ ያስፈልጋል አልኩኝ፡፡ ይኼንን ሁሉ እስር ቤት ሆኜ ነው መገምገም የቻልኩት፡፡
ሪፖርተር፡- ይቅርታ በጠየቁበት ቦታ ላይ “በጎ ነገርም እንደተሠራ ሁሉ…” ያሉት አባባል አለ፡፡ በደርግ ሥርዓት ጊዜ ጦርነቱና ግድያው እንጂ በጎ ነገር የሚታያቸው በጣም ጥቂት ሰዎች ብቻ ናቸው፡፡ እንዴት ነው የሚያስረዱን?
ሌ/ኮ ፍሰሐ፡- በመጀመሪያ ደረጃ የመሬት አዋጅ እንዲሁ እንደ ቀላል ነገር የሚወሰድ አይደለም፡፡ በኢትዮጵያ ውስጥ ኢኮኖሚያዊ፣ ማኅበራዊና ፖለቲካዊ ለውጥ ያመጣ ነው፡፡ ሥር ነቀል ለውጥ ነበር፡፡ የነበረውን ሥርዓት በሙሉ ለወጠው፡፡ በአገራችን ለመጀመሪያ ጊዜ የእኩልነት መንፈስም ያሰፈነ ነው፡፡ በዚህም ውስጥ ገበሬዎችና ሴቶች ተደራጅተው የሚጠቀሙበት የገበሬዎች ማኅበር የሚቋቋምበት ትልቅ ለውጥ ነው ማለት ይቻላል፡፡ ቀጥሎ የመሠረተ ትምህርት ነው፡፡ 93 በመቶ ሕዝብ መኃይም በሆነበት አገር ሶሻሊዝም አካሂዳለሁ ማለት ቅዠት ነው፡፡ ያንን መኃይምነት ለማጥፋት በከፍተኛ ደረጃ መንግሥት ተረባርቧል፡፡ በዚያ መረባረብ መኃይምነት ከ93 ወደ 36 በመቶ ድረስ እንዲወርድ ተደርጓል፡፡ ከአንዴም ሁለቴ ከዩኔስኮ ሽልማትም ተገኝቷል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ዛሬ የከተማ ልማት የሚካሄድበት ሁሉ ከአዋጅ ውጪ መሬት ወርሰን ባስቀመጥነው ነው። ይኼ መንግሥትም ተጠቃሚ ነው፡፡ የመንግሥት ቦታ ባይወረስ ኖሮ ገና አንድ አብዮት ያስፈልገው ነበር፡፡ ስለዚህ ለልማት አመቺ ሁኔታ ተፈጥሯል ማለት ነው፡፡
ከዚህ ባሻገር ጦርነት እየተዋጋንም ቢሆን ብዙ ፋብሪካዎች፣ ለምሳሌ (የኤሌክትሪክ ኃይል ማመንጫዎች) እና የልማት ሥራዎች ተሠርተዋል፡፡ ለምሳሌ በጅምር የነበሩና ገንዘብ በማጣት ተጠንተው የተቀመጡ ብዙ ፕሮጀክቶች ነበሩ፡፡ የጨርቃ ጨርቅ ፋብሪካዎች ስንወስድ የአርባ ምንጭ ጨርቃ ጨርቅ ፋብሪካ፣ የኮምቦልቻ ጨርቃ ጨርቅ ፋብሪካ፣ እንዲሁም የመልካ ዋከና የኤሌክትሪክ ኃይል ማመንጫ ግድብ፣ የፊንጫ የማስፋፋት ሥራ፣ ጣና በለስና ሌሎች ያን ጊዜ የተሠሩ ናቸው፡፡ የመከላከያ ኢንዱስትሪ ኮሚሽን ጋፋት ላይ ተቋቁሞ ጠመንጃ ማምረት የጀመረበት ጊዜ ነበር፡፡ አሥር ሺሕ ጠመንጃ በዓመት የሚያመርትበት ጊዜ ነበር፡፡ ስለዚህ ከባዶ ተነስቼ ሳይሆን ከጦርነቱ ጎን ለጎን ብዙ ፕሮጀክቶች ተከናውነው ነበር፡፡ ነገር ግን ጦርነቱ በማየሉ የገንዘብ እጥረትም ስለነበር እንጂ ብዙ ፕሮጀክቶች በጥናት ላይ የነበሩም ነበሩ፡፡ የቀለበት መንገድ፣ የከተማ ባቡር መስመር ተጠንቷል፡፡ ከአሰብ-አዲስ አበባ የባቡር መስመር ተጠንቷል፡፡ ግን በወቅቱ ገንዘብም አልተገኘም። ጦርነቱም አልፈቀደም እንጂ በልማት በኩል የማይናቅ አስተዋጽኦ ተደርጓል፡፡ የነበረውን መካድ አይቻልም፡፡ ከነበረው መቀጠል ግን ተገቢ ነው፡፡
ሪፖርተር፡- “ከነበረው መቀጠል ተገቢ ነው” ሲሉ ምን ዓይነት ኢትዮጵያ ተገንብታ ማየት ነው የሚፈልጉት?
ሌ/ኮ ፍሰሐ፡- ማንም ኢትዮጵያዊ ቢሆን የበለፀገች ኢትዮጵያን ማየት ይፈልጋል፡፡ ከመኃይምነት የተላቀቀችና የሕግ የበላይነት የሰፈነባት ኢትዮጵያን ማየት ይፈልጋል፡፡ የነፃነት አገር እንድትሆን (ፕሬስን ጨምሮ) ማየት ነው የምመኘው፡፡
ሪፖርተር፡- ከሥርዓቱ አወቃቀር አንፃር የእናንተ አሀዳዊ መንግሥት ነበር። በእሱ ምትክ የተጀመረው የፌዴራል ሥርዓት አወቃቀር ፕሮጀክት ላይሳካ ይችላል ብለው ይጠረጥራሉ?
ሌ/ኮ ፍሰሐ፡- ከባድ ጥያቄ ነው፡፡ ዩኒቨርሲቲ ውስጥ እንቅስቃሴ በነበረበት ወቅት ተማሪው ለሁለት የተከፈለ አመለካከት የነበረው። ይኼ አስተሳሰብ ከፊሉ ኢትዮጵያ ውስጥ ያለው ችግር የብሔር ብሔረሰብ ጥያቄ ነው ይላል፡፡ ከፊሉ ደግሞ የመደብ ጥያቄ ነው ይላል፡፡ የመደብ ነው ያሉት በኅብረ ብሔርነት ተደራጅተው ትግላቸውን ቀጥለዋል፡፡ ሌሎች ደግሞ በብሔር ተደራጅተው የብሔር ነፃነት ሲያራምዱ ነበር፡፡ ዛሬም ይኼ አስተሳሰብና አመለካከት እንዳለ ነው፡፡ ምን ይሻላል? ምን ይሆናል? የሚለው እንግዲህ ጊዜና ታሪክ ሁሉ እየፈታው የሚሄድ ይሆናል፡፡ “ያጠናክረናል ወይስ ያፈርሰናል?” የሚለውን አሁን መተንበይ ይከብደኛል፡፡ ገና መገምገም ያስፈልገኛል፡፡ አሁን አስተያየት ከሰጠሁ የችኮላ አስተያየት ነው የሚሆነው፡፡
ሪፖርተር፡- አንዳንድ ሰዎች ብሔራዊ ዕርቅ እንዲደረግ ይጠይቃሉ፡፡ ነገር ግን በግልጽ ያጠፉትን እንኳን አሜን ብለው አይቀበሉም፡፡ ይቅርታም አይጠይቁበትም፡፡ የበደለ ሲክድ ተበዳይን የባሰ ቂሙን እንዳይረሳ አያደርገውም?
ሌ/ኮ ፍሰሐ፡- በመሠረቱ አንድ ግልጽ መሆን ያለበት ነገር አለ፡፡ መድረክ ይዘጋጅ ሲባል መጨረሻ መጽሐፌ ላይ እንዳሰፈርኩት የሠራናቸውን ጥፋቶች የምንናዘዝበት፣ ድክመቶቻችንም ለኢትዮጵያ ሕዝብ የምንነግርበት ማለታችን ነው፡፡ “እውነት አፈላላጊና ዕርቅ” ማለት ጥፋቱንም ይሁን ልማቱን ተናዝዘን ከዚያ በኋላ ነው ዕርቅ የሚመጣው ብዬ ነው የማምነው፡፡ በአብዮቱ ውስጥ ተዋናይ የነበሩት እያንዳንዳቸው ያደረጉት ነገር ካለ ጥፋታቸውን ተናዘው፣ ለኢትዮጵያ ሕዝብ ተናግረው ነፃ ይሁኑ ነው፡፡ ካልሆነ ተመልሶ ወደዚያው ነው፡፡
ሪፖርተር፡- ለአንዳንድ ሰዎች የጄኔራል አማን ሚካኤል አምዶም መገደል፣ ለሌሎች ደግሞ የግንቦት ስምንቱ መፈንቅለ መንግሥት መክሸፉ ለኤርትራ መገንጠል እንደ ዋና ምክንያት ያቀርባሉ፡፡ የእርስዎ አስተያየት ምንድነው? ለምሳሌ “ጄኔራሎቹ ባይገደሉ ኖሮ ኤርትራ አትገነጠልም ነበር” ይላሉ?
ሌ/ኮ ፍሰሐ፡- ሁለቱንም ለይቼ ነው የማያቸው፡፡ በወቅቱ ጄኔራል አማን አምዶም በኤርትራ ሕዝብ ከፍተኛ ተቀባይነት አግኝተው ነበር፡፡ እርግጥ ነው ሻዕቢያ [የዚያን ጊዜ ቋንቋ ነው የምጠቀመው] ሆነ ጀብሃ የጄኔራል አማን መኖርን በጣም ነበር የተቃወሙት፡፡ ሕዝቡን ይዞብናል በሚል። እሳቸውን ለማስወገድ ብዙ ጥረት አድርገዋል፡፡ ጄኔራል አማን በነበራቸው የሕዝብ ተቀባይነት የሱዳን መንግሥትም ሆነ ሌሎች የዓረብ አገሮችም ለመርዳት ዝግጁ ስለነበሩ ለኤርትራ ጉዳይ መፍትሔ ለመስጠት ተዘጋጅተው ነበር፡፡ ይኼ ያመለጠ ዕድል ነው፡፡ ጀኔራል አማንን ደርግ ሲገድላቸው ኤርትራንም ጭምር አብሮ ነው የገደለው፡፡ የግንቦት ስምንት መፈንቅለ መንግሥት በወቅቱ በ1981 ዓ.ም. መካሄድ ነበረበት ወይ? ጦርነቱ ተፋፍሞ ትግራይ ላይ ጦራችን ተሸንፎ፣ ኤርትራም ላይ አፍአቤት እንደዚሁ ውድቀት አጋጥሞ፣ በዚህ መሀል መፈንቅለ መንግሥት ማድረግ ጥቅሙ ለማን ነበር? ለእነዚህ የፖለቲካ መፍትሔ እናመጣለን የሚሉት የዋህነት ይመስለኛል፡፡ መጽሐፌ ላይ አስቀምጬዋለሁ፡፡ ምክንያቱም ሻዕቢያ ሁለት ስለት ይዞ ነው የተንቀሳቀሰው፡፡ እነዚህ ሰዎች ተሳክቶላቸው መንግሥትን ቢቆጣጠሩና እርስ በርስ ቢተራመሱ ወይም ደግሞ የሰከነ ሁኔታ እስኪፈጠር ድረስ እኔም ተጠቃሚ ነኝ የሚል ነው፡፡ እነሱ ደግሞ ቢወገዱ መንግሥት ስለሚዳከም አሁንም ተጠቃሚ እንደሚሆን ነው፡፡ የሆነው ይኼው ነው፡፡ እነዚያ ሁሉ ጄኔራል መኮንኖች ናቸው የተሳተፉት፡፡ እነሱም ተወገዱለት፡፡ ከሁለቱ አንዱ ተሳክቶለታል፡፡ በአንፃሩ ሕወሓት ግን መፈንቅለ መንግሥቱን አልተቀበለም፡፡ አልተባበረም፡፡
ሪፖርተር፡- ምክንያቱ?
ሌ/ኮ ፍሰሐ፡- እሱን ራሳቸው እነሱ ናቸው የሚነግሩህ፡፡ አዲስ መንግሥት መጥቶ ምን እንደሚሆን ስላላወቁ ሊሆን ይችላል፡፡ አንድ ወታደራዊ መንግሥት በሌላ ወታደራዊ መንግሥት ቢለወጥ ምን ለውጥ ያመጣል የሚል ሐሳብ የነበራቸው ይመስለኛል፡፡
ሪፖርተር፡- በሕወሓት ቦታ ሆነው ሲያዩት ትክክለኛ አቋም ነበር?
ሌ/ኮ ፍሰሐ፡- በእኛ ቦታ አይደለም [ሳቅ] በሕወሓት ቦታ ሆኜ … ትክክል ነበር…
ሪፖርተር፡- ተያያዥ ጥያቄ ላንሳ፡፡ በሻዕቢያና በደርግ መካከል ተከታታይ ድርድሮች ተደርገዋል ይባላል፡፡ እንዴት ነበር የተቋጩት?
ሌ/ኮ ፍሰሐ፡- መጀመሪያ ነገር በሁለቱም በኩል ቅን መንፈስ አልነበረም፡፡ ሻዕቢያ ወታደራዊ የበላይነቱ ሲያገኝ ድርድሩን ያቀዘቅዛል፡፡ ደርግም የበላይነቱን ሲያገኝ እንደዚሁ ያቀዘቅዛል፡፡
ሪፖርተር፡- ለምን ያህል ጊዜ ነበር የተካሄዱት?
ሌ/ኮ ፍሰሐ፡- ብዙ ጊዜ ነው የተካሄዱት፡፡ በሩሲያ፣ በጀርመን፣ በጣሊያን፣ እንዲሁም በየመን በኩል ሙከራዎች ተደርገዋል፡፡ ውስጥ ለውስጥ በርካታ ድርድሮች ተካሂደዋል፡፡ ስምምነት ላይ ግን መድረስ አልተቻለም፡፡ በመጨረሻ በሕገ መንግሥቱ ውስጥ ልዩ ራስን በራስ የማስተዳደር [ራስ ገዝ] ሥልጣን ለኤርትራም ለትግራይም ተሰጥቶ ነበር እሱም አልሆነም፡፡ በእርግጥ በሕወሓትና በሻዕቢያ መካከል ብዙ ጥርጣሬዎች እንደነበሩ አውቃለሁ፡፡
ሪፖርተር፡- የሁለቱንም (የሕወሓትና የሻዕቢያ) የአደረጃጀት፣ የስትራቴጂና የውጊያ ስልት ሳነብ የተለያዩ ሆነው ነው የማገኛቸው፡፡ በእርግጥ ሕወሓት ሲመሠረት ካሻዕቢያ መጠነኛ ድጋፍ ተደርጎለታል፡፡ ሕወሓት ሙሉ ለሙሉ በሻዕቢያ ተጠፍጥፎ የተሠራ የሚመስላቸው ሰዎችም ቀላል አይደሉም፡፡ እናንተ በወቅቱ የምትሉት ነገርም ነበር። የምታውቁት እውነት ምን ነበር?
ሌ/ኮ ፍሰሐ፡- በደርግ ዘንድ ብዙ ጊዜ አንድ ስትራቴጂ ነበር፡፡ በተለይ ፕሬዚዳንቱ ዋናው የኢትዮጵያ ጠላት ሻዕቢያ ነው ብለው ነበር የሚያምኑት፡፡ ስለዚህ ትኩረቱ ሁሉ ሻዕቢያ ላይ ነበር፡፡ ሌሎች ሁሉ የእሱ ፍጡራን ስለሆኑ በራሳቸው ይሞታሉ የሚል ግምት ነበራቸው፡፡ ሁለተኛ የወቅቱ የሕወሓት እንቅስቃሴን በተመለከተ ትግራይ ወዴት ይሄዳል? የሚልም ነበር፡፡ አንደኛ ኢትዮጵያዊ ነው፡፡ የኢትዮጵያ መሠረት ነው፡፡ ወዴት ተገንጥሎ ይሄዳል? ሁለተኛ እነዚህ ሰዎች (ሕወሓቶች) የሚሉትን ሕዝቡ አይቀበላቸውም የሚል ዕምነት ፕሬዚዳንቱ ስለነበራቸው እንደ ሁለተኛ ደረጃ ነበር የሚታየው፡፡ ስለዚህ ድርድሩ ብዙ ጊዜ ከሻዕቢያ ብቻ ነበር የቀጠለው እንጂ ከሕወሓት ጋር አልነበረም፡፡ አንድ ጊዜ ብቻ በእኔ በኩል ግንኙነት እንዲደረግ ተባለ፣ ያ ብዙም አልሄደም፡፡ ዋናው ነገር ለዚህ ሁሉ መንስዔ፣ ለጦርነቱ ሁሉ መነሻ ሻዕቢያ ነው የሚል ነበር፡፡ ሻዕቢያ ከሞተ ሌሎች ይሞታሉ የሚል ግምገማ ነበር፡፡ በዚህ ስትራቴጂ ሕወሓት ብዙ ትኩረት እንዳያገኝ ይደረግ ነበር። ያ ስትራቴጂ ትክክል ነው አይደለም የሚለው ያከራክራል፡፡
ሪፖርተር፡- በሕወሓትና በሻዕቢያ መካከል የነበረውን ግንኙነት በተመለከተ፣ ሻዕቢያ ሕወሓትን ብዙ እንደረዳው ብቻ ነው የሚነገረው፡፡ አንዳንዶች ደግሞ በተቃራኒው ይናገራሉ። ካለዎት ተጨባጭ መረጃ እውነቱ የቱ ነው?
ሌ/ኮ ፍሰሐ፡- እንዴ! በቀይ ኮከብ ዘመቻ ጊዜ [በሳህል ተራሮች] ማነው ይህንን ሁሉ ጦርነቱ ወደ ማክሸፍ ያደረሰው? ይኼ እኮ ግልጽ የሆነ ነገር ነው፡፡ ሦስት ብርጌድ ጦር ልኮ ያንን የጦርነት ገጽታ የለወጠው ሕወሓት ነው፡፡ ሻዕቢያ እኮ ጓዙን ጠቅልሎ ወደ መሄድ የደረሰበት ጊዜ ነበር፡፡ ሱዳን ለመግባትና ከዚያም ወደ ሽምቅ ተዋጊነት ለመቀየር የነበረውን ሁኔታ የለወጠው ሕወሓት ነው፡፡ ሁለቴም ሦስቴም ሕወሓት አብሮ ከኤርትራ ጋር ደርግን ወግቷል፡፡ ብዙ ጊዜ እንዲያውም ሻዕቢያን ከውድቀት ያዳነው ሕወሓት ነው፡፡ ታሪኩ ሊካድ ይችል ይሆናል፡፡ እኔ እስከማውቀው ድረስ ግን በታሪክም በማስረጃም የተረጋገጠ ነው፡፡ በቀይ ኮከብ ዘመቻም በሌላም ሕወሓት ሄዶ ተዋግቷል፡፡ ሕወሓት የተዋጋው በርዕዮተ ዓለም አንድነት ነው ወይ? ሁለቱም ደርግ ጠላታችን ነው ከሚል መንፈስ የተነሳ ብቻ ነው፡፡ እንዲያው አንዳንድ ጊዜ ሻዕቢያ ከደርግ ጋር ድርድር ሲያደርግ ሕወሓት ላይ ብዙ ችግርና ጭቅጭቅ እንደነበር መረጃዎች ነበሩን፡፡ በእርግጥ ሻዕቢያ በሽሬ ጦርነት መሳተፉን በድምፀ ወያነ ሰምቼያለሁ፡፡ ምን ያህል እንደሆነ ግን ግርድፍ መረጃ ነው ያለኝ፡፡
ሪፖርተር፡- ሌ/ኮ መንግሥቱ ኃይለ ማርያም “አገር ጥለው እስከሄዱ ድረስ አገር ወዳድ ነበሩ” በመጽሐፍዎ ያሉት ነገር አለ፡፡ ያ ሁሉ ግድያና ያ ሁሉ ዕልቂት ተፈጽሞ የሥርዓቱ ዋና ቁንጮ ሰው ‘አገር ወዳድ ነበር’ ለማለት ምንድነው መለኪያው? እንደ አፄ ዮሐንስም ሆነ እንደ አፄ ቴዎድሮስ አንገቱን ለአገሩ ያልሰጠ መሪ በምን መሥፈርት ነው አገር ወዳድ ማለት የሚቻለው? መጨረሻ አካባቢም ቢሆን ዘርን መሠረት ያደረጉ፣ “ትግራይ ጠመኔ መግዛት አይችልም…”፣ “ሰሜን ሸዋ ሲዘምት እንጂ ሲዘመትበት…” የመሳሰሉ አንዱን ሕዝብ በሌላው ላይ እንዲነሳ የሚቀሰቅሱ ጉዳዮች ነበሩ፡፡
ሌ/ኮ ፍሰሐ፡- መጽሐፉ ውስጥ እነዚህን ንግግሮች በሙሉ ጠቅሻቸዋለሁ፡፡ ሽሽቱን ጨምሮ በመጨረሻ ሕዝባዊ አመኔታቸው እየመነመነ አምባገነንነታቸው እየገዘፈ ሄደ ብያለሁ፡፡ ይኼ የሚያሳይህ የነበራቸው ሕዝባዊነት እየተሟጠጠ፣ ሥልጣናቸውን ብቻ ማየት እንደጀመሩ ነው፡፡ በፊት ሕዝባዊ አመለካከት ነበራቸው፡፡ በመጨረሻ ባያበላሹት ያልኩት አሁን ያልከውን “የትግራይ ሕዝብ ጠመኔ መግዥያ የለውም” ወዘተ ብለዋል። አገር ወዳድም፣ ራስ ወዳድም ብያለሁ፡፡ ሁለቱም ይቃረናሉ፡፡ አገር መውደድ እንግዲህ ሕዝባዊ አመለካከት መኖር ነው፡፡ በመሠረቱ የፖለቲካ መፍትሔ ባለማምጣታቸን እንወቀስ እንደሆነ እንጂ ግድያን እኛ ያመጣነው አይደለም፡፡ ሕወሓትንም፣ ሻዕቢያንም እኛ አልፈጠርናቸውም፡፡ ቀይ ሽብርና ነጭ ሽብርን ማን እንደጀመረው ግልጽ ነው፡፡ በእነዚህ ሁሉ ሰው ስለተገደለ ሕዝባዊ አመለካከት አልነበራቸውም ማለት አይቻልም፡፡ በሶማሊያ ጦርነት ሚሊሺያ በማደራጀት እንዴት ተደርጎ ያንን ወረራ በቀላሉ እንዲገታ ማድረግ በመቻል የእሳቸው አስተዋጽኦ ከፍተኛ ነበር፡፡ አገራቸውን ስለሚወዱ ነው፡፡ ነገር ግን መጨረሻ ላይ ራሳቸውን ወደዱ፡፡
ሪፖርተር፡- “በመጨረሻ ባያበላሹት” የሚለው ሁሉንም ነገር አያበላሸውም? አፍአዊ እንጂ አገር ወዳድ እንዳልነበሩ ማሳያ አይደለም ወይ?
ሌ/ኮ ፍሰሐ፡- እኔ እስከዚያ ድረስ “አገር ወዳድ ናቸው” ብዬ አምን ነበር፡፡ “በመጨረሻ ግን አበላሹት” ስል “አገር ወዳድ አልነበሩም” ማለት ነው፡፡ [ሳቅ]
ሪፖርተር፡- አሁንም ድረስ ግን ፕሬዚዳንቱ በመጽሐፋቸውም በንግግራቸውም “ጉልበታቸው” እንዳለ ነው፡፡ ምንም የሚፀፅታቸው ነገር ያለ አይመስልም፡፡
ሌ/ኮ ፍሰሐ፡- መቼም ይኼ እንዳልፀፀታቸው መናገር በእሳቸው ጫማ ሆኜ እንደ መናገር ነው፡፡
ሪፖርተር፡- እንደ ሥርዓት ሲያዩትስ?
ሌ/ኮ ፍሰሐ፡- እንግዲህ እያንዳንዱ ሰው ይለያያል፡፡ ይኼ ግትር ጠባያቸው ነው ለውድቀትም የዳረገን፡፡ አሁንም ከገንጣይ አስገንጣይ ጋር ነው ወይ የምደራደረው ይላሉ፡፡ ድሮም የምትደራደረው ከሚቃወምህ ነው እንጂ አንተን ተከትሎ ከሚሄድ ሰው ጋር አይደለም፡፡ ስለዚህ የፖለቲካ መፍትሔ ማምጣት ያልተቻለው በእሳቸው ግትር ፀባይ ነው፡፡ እንደዚያ መሆኑን አስቀምጬዋለሁ፡፡
ሪፖርተር፡- “አንድ ሰው ብቻውን አምባገነን አይሆንም” የሚል አስተሳሰብም አለ።
አጠገባቸው የነበራችሁ ሰዎች የእሳቸውን አምባገነንነት ስታዩ “ያላደረግነው” በማለት የሚፀፅትዎ ነገር አለ?
ሌ/ኮ ፍሰሐ፡- አንደኛ ሥርዓቱ ለአምባገነንነት ይመቻል፡፡ የአንድ ፓርቲ ሥርዓት ነው፡፡ የአንድ ፓርቲ ሥርዓት በተለይ በሶሻሊዝም ደግሞ የሚመራ ለአምባገነንነት የተመቸ ነው፡፡ ስለዚህ ይኼ ሁኔታ የእሳቸውን አስተሳሰብ የሚደግፍ አልነበረም ማለት አይደለም፡፡ እስከተወሰነ ደረጃ ሁላችንም ደግፈናቸዋል፡፡ አብረን ነበር የምንጓዘው፡፡ ቀስ በቀስ ሁኔታዎች እየተቀያየሩ ሄዱና ምንም የማታደርግበት ሁኔታ ላይ ትደርሳለህ፡፡ ይኼ በሌሎችም አገሮች የታየ ነው፡፡
ምንጭ ሪፖርተር ጋዜጣ